በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ! አሜን፡፡







በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከኦሮሚያ እና ብሔር ብሔረሰቦች ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተሰጠ መግለጫ፡፡
‹‹በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ፡፡›› የሐዋርያት ሥራ ም 20፡28
በሐዋርያዊ ትውፊት መሠረት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመጀመሪያውን ጳጳስ ያገኘችው በ325 ዓ.ም. የግብጽ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ከነበሩት ቅዱስ አትናቴዎስ በአክሱም ነገሥታት ጳጳስ እንዲሾም በተጠየቀ ጊዜ በአክሱም ቤተ-መንግሥት ያደገው እና የማኅበረሰቡን ቋንቋ፣ ባህል እና እሴት የሚያውቅ አባ ፍርምናጦስን አቡነ ሰላማ ብሎ በመሾም ነበር፡፡
በኋላም እግዚአብሔር ተሥዓቱ ቅዱሳንን ወደ ኢትዮጵያ በመላክ ወንጌል በስፋት በሀገራችን እንዲሰበክ አድርጓል፡፡ ነገር ግን የግብጽ ቤተ ክርስቲያን ኢትዮጵያ ከራሷ ልጆች ጳጳስ እንዳትሾም በመከልከልዋ ምክንያት ካህናት እና መምህራነ ወንጌል ጠፍተው ምዕመናን ወደ ባዕድ አምልኮት በተመለሱ ጊዜ የምህረት እጁ በክፉዎች ተንኮል የማይታሰር እግዚአብሔር ከኢትዮጵያ ምድር ጻድቁ አቡነ ቅዱስ ተክለ ሃይማኖትን፡ አስነስቶ በሀገራችን ልዩ ልዩ ቋንቋዎች በመጠቀም ታላቅ ሐዋርያዊ ገድል እንዲጋደሉ፣ ገዳማትን እንዲገድሙ፣ ብዙ ቅዱሳን ደቀ መዛሙርትን እንዲያፈሩ፣ ካህናት እና ዲያቆናት እንዲሾሙ እና የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን እንድታገግም እንዲሁም ምእመናን ወደ ንስሐ እንዲመለሱ አድርጓል፡፡
ዛሬ ከምስራቅ እስከ ምዕራብ ከሰሜን እስከ ደበብ፡ የሀገራችን ክፍሎች ከዚያም ባሻገር የሚታዩ የአባታችን አሻራ የእግዚአብሐር ድንቅ ሥራ ምስክር ነው፡፡
በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ንጉሰ ነገሥት ንግሥና ዘመን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከግብፅ ቤተ-ክርስቲያን ተጽዕኖ ወጥታ የራስዋን ጳጳሳት እና ፓትርያርክ መሾም ጀመረች፡፡ በዚህም ምክንያት የግብጽ ቤተ ክርስቲያን ቀኖና ተጣሰ በማለትዋ ምክንያት በሁለቱ አሀት አብያተ ክርሰቲያናት መካከል ለረጅም ዘመናት መራራቅ እና መቃቃር እንደነበር የአደባባይ ምስጢር ነው፡፡ ሆኖም የንጉሠ ነገሥቱ መንግሥት በሚከተለው አንድ ሀገር አንድ ቋንቋ ፖሊሲ በገዥ መደብ እና ቤተ ክርስቲያን አለቆች ስምምነት ከግዕዝ እና ከአማርኛ ቋንቋ በቀር ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል አልተፈቀደላትም፡፡ ይህም የሆነው ከአንድ ጎሳ የሚወለዱ የቤተ መንግሥት እና የቤተ ክህነት ገዥዎችን የጥቅም ክፍፍል ለማስቀጠል ነበር፡፡ ለዘመናት ቤተ ክርስቲያን የራሷን ልጆች በእራሷ ለመሾም ስትናፍቅ የነበረው የጵጵስና ሹመት የወንጌል
አገልጋይነት ሥራ መሆኑ ቀርቶ በጠቅላይ ግዛት ቤተ ክርስቲያን የሚያስተዳድሩ እና ቡራኬ የሚሰጡ ኤጵስቆጶሳት ሹመት ሆነ፡፡ ስለሆነም ባለፉት ሰባ ዓመታት የተደራጀው የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት እና የጳጳሳት ሹመት የወንጌል አገልግሎት ለብሔር ብሄረ ሰቦች በቋንቋቸው ማድረስ ሳይሆን በአብዛኛው የበለጠ ሥጋዊ ሀብትን ለማደላደል በሚፈልጉ ኤጵስቆጶሳት እየተሞላች መጥታለች፡፡
ይህ አካሄድ ቀስ በቀስ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ምእመናንን ለቤተ ክርስቲያናቸው እንግዳ እንዲሆኑ እና ከቤተ ክርስቲያን እንዲርቁ እያደረገ መጣ፡፡ ይልቁንም ዘመናዊ ትምህርት የመማር እድል ያገኘውን ትውልድ የአባቶቹን ሃይማኖት ትቶ በብዛት ወደ ሌሎች ቤተ እምነት እንዲገባ አድርጎታል፡፡ በተለይም ባለፉት ሰላሳ አንድ ዓመታት የኢትዮጵያ መንግሥት በሚከተለው የትምህርት ፖሊሲ እና አስተዳደር ዘይቤ የተነሳ አብዛኛው የኦሮሚያ እና የሌሎች ክልል ተወላጆች በእናት ቋንቋቸው ስለሚማሩ በአማርኛ ብቻ የሚሰጡ አግልጎሎቶችን በትክክል ማወቅ እና መረዳት አልተቻላቸውም፡፡ ስለሆነም ብዙዎች የመጀመርያውን እና ትክክለኛዋን ሃይማኖታቸውን ትተው በሚያውቁት ቋንቋ ወደሚሰበክበት ሌሎች ቤተ እምነታት እየኮበለሉ ይገኛሉ፡፡ ከዚህም የተነሳ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አማኞች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ በአስደንጋጭ ሁኔታ እየቀነሰ መጥቷል፡፡
ከላይ የተዘረዘሩትን የቤተ ክርስቲያን ተግዳሮት ለመቅረፍ እናበማርቆስ ወንጌል ምዕራፍ 16፡16 ጌታ #ወደ ዓለም ሁሉ ሂዱ ወንጌልን ለፍጥረት ሁሉ ስበኩ$ በሚለው አምላካዊ ትእዛዝ መነሻነት እንዲሁም ቅዱስ ጳዉሎስ በሮሜ መልዕክቱ ምዕ : 10 :14# እንግዲህ ያላመኑበትን እንዴት አድርገው ይጠሩታል?ባልሰሙትስ እንዴት ያምናሉ ያለ ሰባኪስ እንዴት
ይሰማሉ? እንዲሁም በራዕይ ዮሐንስ ም 5 ቁ. 9 -10 ላይ <<ከነገድም ሁሉ ከቋንቋም ሁሉ፣ ከወገንም ሁሉ፣ ከሕዝብም ሁሉ ሰዎችን ዋጅተህ ለአምላካችን መንግሥት እና ካህናት ይሆኑ ዘንድ አደረግሃቸው፡፡›› ተብሎ ቅዱሳን ሐዋርያት የተመሰገኑበትን ሥራ እና ሕይወት
ለማስቀጠል፤ በዮሐንስ ወንጌል፡- ም 10፡-11 መልካም እረኛ እኔ ነኝ፤ መልካም እረኛ ነፍሱን ስለበጎቹ ያኖራል፤ እረኛ ያልሆነው በጎቹም የእርሱ ያልሆኑ ምንደኛ ግን ተኩላ ሲመጣ ባየ ጊዜ
በጎቹን ትቶ ይሸሻል .... በጎቹንም ይበትናቸዋል፡፡ ያለውን የጌታን ማስጠንቀቂያ በማስተዋል፤እንዲሁም በምዕራፍ 21፡15 ጌታችን ስምዖን ጴጥሮስን #የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ ትወደኛለህ ብሎ በተደጋጋሚ ሶስት ጊዜ ከጠየቀው በኋላ በመጨረሻም ከወደድከኝ ጠቦቶቼን ጠብቅ ... ግልገሎቼን ጠብቅ፣ . . . በጎቼን አሰማራ እንዳለው እኛም ይህን አምላካዊ ትዕዛዝ እንዲፈጸም ከልብ በመሻት እና ከመንፈስ ቅዱስ የተቀበልነውን መንጋውን የመጠበቅ አደራ ለመወጣት፤
እንዲሁም በነቢዩ ሕዝቅኤል ም 34 ቁጥር 3 እስከ ፍጻሜው‹‹ ራሳቸውን ለሚያሰማሩ እረኞች ወዮላቸው፤ እረኞች በጎችን ያሰመሩ ዘንድ አይገባቸውምን? ጮማውንም ትበላላችሁ፣
ጠጉሩንም ትለብሳላችሁ፣ የወፈሩትን ታርዳላችሁ፣ በጎቹንም አታሰማሩም፤ የደከመውንም አላጸናችኁምም፣ የታመመውንም አላከማችሁትም፣የተሰበረውንም አልጠገናችሁትም፣ የባዘነውንም አልመለሳችሁትም፣ የጠፋውንም አልፈጋችሁትም፣ በኃይል እና በጭቆናም ገዛችዋቸው፣ . . ..እረኛንም በማጣት ተበተኑ፣ ለምድርም አራዊት ሁሉ መብል ሆኑ፡፡››
የሚለውን በቅዱሳን ነቢያት አድሮ እግዚአብሔር የተናገረውን ማስጠንቀቂያ በማስተዋል እንዲሁም
ቅዱሳን አበው በመጽሐፈ ፍትህ መንፈሳዊ አንቀጽ 5፤ ንዑስ አንቀጽ 138 ‹‹ኤጲስ ቆጶስ ሆይ ከበጎች የተለየህ ብትሆን ጠላታቸው አንተነህ፤ የእግዚአብሔር ባላጋራው (ጠላት) አንተ ነህ፡፡እግዚአብሔር ጠባቂ የሆናቸውን በጎች የምታጠፋ አንተ ነህ፡፡ እኛ ብዙ ቋንቋዎችን
በመናገር በድካም በትጋት እና በጾም ከመሬት ላይ በመተኛት እና በመሰደድ፣ በመታሰር እና ዘወትር በመታመም ከብዙ ነገድ ውስጥ የሰበሰብናቸውን ምእመናንን አንተ እንዴት ትበትናለህ? እነርሱም የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ጉባኤ ናቸው፡፡›› ብለው ያሳሰቡን የቀኖና ቃል መሠረት
እራሳችንን ከፍርድ ለማዳን እንዲሁም ከበጎች ላለመለየት ብፁዓን አባቶች ቅዱስ ሲኖዶስን መሥርተን ኤጲስ ቆጶሳት በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ቀብተን መድበናል፡፡ ይህ የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በምትቀበለው ፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቁጥር 105 እንዲህ ሲል በሚያዘው መሠረት ኤጵስ ቆጶስ ከሶስት ኤጲስ ቆጶሳት ይሾም ዘንድ እናዛቸዋለን፡፡ የችግር ዘመን ቢሆን ግን ከሁለት ኤጲስ ቆጶሳት ይሾም ....የሁለት እና የሶስት ምስክርነት የጸና ይሆናልና፡፡
ስለሆነም የመንፈስ ቅዱስን ፈቃድ ከማዳመጥ ይልቅ በጥቂት ሊቃነ ጳጳሳት አሳሳችነት በቅዱስ
ሲኖዶስ በእኛ ላይ የተላለፈው ውግዘት ንጉሥ ሰሎሞን በመጽሐፈ ምሳሌ ም 26 ቁጥር 2 ‹‹ እንደሚተላለፍ ድንቢጥ ወዲያና ወዲህም እንደሚበርር ጨረባ ከንቱ እርግማን በማንም ላይ አይደርስም›› እንዳለው የተለለፈው ውግዘት እንዲሁ ባዶ ነው፡፡
ነገር ግን የውግዘቱ ዓላማ እኛ ሦስቱን ሊቃነ ጳጳሳት እና 25 ኤጲስ ቆጶሳት ላይ የተላለፈ ብቻ ሳይሆን ለቤተ ክርስቲያን የሚቆረቆሩ እና ለቤተ ክርስቲያን የሚተጉትን ካህናት፣ ዲያቆናት እና ምእመናንን ከቤተ ክርስቲያን አርቆ በቤተ ክርስቲያን ውድቀት የተለመደ ሥጋዊ ምቾታቸውን እና ጎጠኛ ፍላጎታቸውን ለመምራት እንዲመቻቸው ነው፡፡ ሆኖም በቅዱስ ሲኖዶስ ስም ለውግዘት ምክንያት ናቸው ተብለው ከተጠቀሱት ነጥቦች ውስጥ ዋና ዋናዎችን እንደሚከተለው አስፈላጊ ግንዛቤ ለማስጨበጥ እንወዳለን፡፡
1ኛ፡ - የእኛ ዓላማ እንደ ከሳሾቻችን የዘር እና የጎሳ ክፍፍል ለመፍጠር ሳይሆን ቅዱሳን ሐዋርያት በፍትሐ ነገሥት አንቀጽ 5 ቁጥር 138 እንደ ገለጹት አባቶቻችን ‹‹ብዙ ቋንቋዎችን በመናገር፣ በድካም፣ በትጋት እና በጾም፣ ከመሬት ላይ በመተኛት እና በመሰደድ፣ በመታሰር
እና ዘወትር በመታመም ከብዙ ነገድ ውስጥ የሰበሰቡአቸውን ምእመናንን ለመጠበቅ የተደረገ የኤጲስ ቆጶሳት ሹመት ነው፡፡
2ኛ፡ - የተሸሙት ኤጲስ ቆጶሳት ምንደኛ ናቸው መባሉ ምንዳኛ ጌታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ
በዮሐንስ ወንጌል ም 10 ቁ. 11 ‹‹ተኩላ ሲመጣ ባየ ጊዜ በጎቹን ትቶ የሚሸሽ፤ .... <በጎቹንም የሚበትናቸው ነው የሚለውን ካለማስታወስ የራሳቸውን ምንደኝነት ለሌላ ለመስጠት እንጂ በጎቼ ወገኖቼ ተኩላ እንዳይበላቸው ብሎ በሃይማኖት የተመሰከረላቸውን ከማሕበረሰቡ ተመርጠው የተሸሙት ሊሆኑ አይችሉም፡፡ እነዚህ የተሾሙት አባቶችም ከሹመታቸው በፊት ቤተ ክርስቲያን በሰጠቻቸው ልዩ ልዩ ታላላቅ ኃላፊነቶችን ሲወጡ የነበሩ እና አገለግሎታቸውም በምእመናን ዘንድ የታወቀ የተመሰከረላቸውም ናቸው፡፡
3ኛ፡ - የቅዱስ ሲኖዶስን ሥልጣን ስለመጋፋት የቀረበው ክስ ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን ለራሳቸው የምንደኝነት ሥራ ለመጠቀም እንዲያመቻቸው የቀረበ ነው፡፡ እኛ ግን ለቅዱስ ሲኖዶስ በቃልም
በጽሑፍም በየጊዜው በቤተ ክርስቲያን ላይ የመጣውን አደጋ ከማሳወቅ እና ከማሳሰብ አልቦዘንም፡፡ የሲኖዶሱን ሥልጣን በማይጋፋ መንገድ በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ንዑስ አንቀጽ 104 በሰጠን ሥልጣን መሠረት የተከናወነ ሢመት ነው፡፡
4ኛ፡- መሠረተ - እምነትን (ዶግማ)፣ ሃይማኖታዊ ቀኖናን እና የአስተዳደር ሥርዓትን የጣሰ ተብሎ የቀረበው ክስ አግባብነት የሌለው እና ሆን ተብሎ ምእመናንን ለማሳሳት እና ግጭት ለመቀስቀስ የተደረገ ውንጀላ ነው፡፡ የተሰጠው ሹመት የቤተ ክርስቲያን መሠረተ - እምነት ሲያጸኑ ለነበሩ እና የበለጠ ለሚያጸኑ አባቶች ነው፡፡ ይልቁንም መሠረተ - እምነት የጣሱት
ቅዱስ ጳውሎስ በሮሜ መልዕክቱ ምዕራፍ 10፡14 #ያላመኑትም እንዴት አድርገው ይጠሩታል፡ ባልሰሙትስ እንዴት ያምናሉ...ያለ ሰባኪስ እንዴት ይሰማሉ›› ብሎ ያስተማረውን ዶግማ የጣሱ እና እየጣሱ ያሉት ናቸው፡፡ ከሳሾቻችን ሹመቱ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን የተደረገ መሆኑን ያውቃሉ፡፡ የሚያስደንቀው ግን ይህንን በቀኖና መሠረት የተደረገውን ያወገዙት
የሲኖዶስ ኣባላት ከቀኖና ውጪ የጵጵስና ሹመት ያደረጉ ሊቃነ ጳጳሳት እንዳሉ እያወቁ በጎጠኞች ድጋፍ ያለፉት መሆናቸው ነው፡፡ ስለዚህ ውግዘቱ ትርጉም የሌለው እና እውነተኞች አባቶች ወደ ቅዱስ ሲኖዶስ እንዳይገቡ ለመከላከል የተደረገ ነው፡፡
5ኛ፡- በአባቶቻችን እና በምእመናን በሕይወትም ሆነ በሞት በማናቸውንም መንፈሳዊ አገልግሎት እንዳያገኙ ተብሎ የተላለፈው ውግዘት ለምእመናኑ ያላቸውን ንቀት በግልጽ ከማሳየቱም በላይ አንድ ሰው በአርባ እና ሰማንያ ቀን ልጅነት
ባገኙባት፤ባደጉባት፤በተማሩባት፤ሀብታቸውን አፍሰው በሰሯት፤ ቤተ ክርስቲያን እንዳይቀበሩና እና መንፈሳዊ አገልግሎት አታግኙ፣ መባሉ ፣ከሃይማኖታዊነት አልፎ ሰብኣዊነትን የሚጋፋ መሆኑን እና ዜግነትን የሰረዘ ህዝቡን ለጥቅም ብቻ የሚፈልጉ ስለመሆኑ ትልቅ ማሳያ ነው፡፡
6ኛ. ቤተ ክርስቲያናችን እራሱን የቻለ ሥርዓተ ውግዘት ያላት እና በሥርዓተ ውግዘቷም መሠረት ተወጋዡ ተጠርቶ ሐሳቡ ከተሰማ እና በሐሳቡም ውስጥ ኑፋቄ የተገኘበት እንደሆነ ተመክሮ እምቢ ሲል ተለይቶ የሚወገዝ ነው፡፡ በዚህ በተያዘው ጉዳይ ላይ ግን በመጀመርያ
የሶስት ቀናት ሱባኤ ከታወጀ በኋላ ሱባኤው ሳይጠናቀቅ እና የመንፈስ ቅዱስን መልስ ሳይጠብቁ እነሱም በመግለጫቸው ላይ እንዳሳወቁት በማኅበራዊ ሚዲያ ጫና ተነሳስተው ተገቢ ያልሆነ ውግዘት አስተላልፏል፡፡ እንዲሁም እራሳቸው እንደገለጹት ውግዘት ካስተላለፉ በኋላ የችግሩን ምንጭ ለማጥናት ኮሚቴ እንዲቋቋም መወሰናቸው የማውገዝ ዓላማቸውን በቶሎ ለመፈጸም እንጂ ችግሩን በትክክል መርምሮ እልባት ለመስጠት አልነበረም፡፡
7ኛ፡ - የግብጽ ቤተ ክርስቲያን ጭምር አውግዛለች መባሉ ለ1600 ዓመታት ቤተ ክርስቲያናችን ከራሷ ልጆች ጳጳሳት ሹማ በሕዝቦችዋ ቋንቋ እንዳታስተምር ማድረጉዋ እየታወቀ፣ በእስራኤል ሀገር የሚገኘውን የዴር ሱልጣን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ገዳማችንን ለመንጠቅ
የሚትታገለንን እንደ ደጋፊ እና ተቆርቋሪ ቆጥሮ የኤጲስ ቆጶሳቱን ምርጫ ተቃወመች መባሉ ምእመናንን ለማሳሳት እና ጥንቱንም የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን እንዳትስፋፋ ያደረገቸውን እንደ በጎ ተግባር መውሰድ ነው፡፡
ኤጵስ ቆጶስ በሀገሩ መስፋት እና መጥበብ በሕዝቡ ማነስ እና ብዛት ምክንያት ከተሾመበት ሀገር ወጥቶ ወደ ሌላ ሀገር አይሂድ ...ከርሷ የሚሻለውን ሊፈልግ አይገባውም፤ ይህ ለእርሱ አይገባም እና፡፡ ለሰው ሁሉ ድርሻ ከእግዚአብሔር ተሰጥቶታል እንጂ፡፡ ይህ ከሕዝባውን ወገን ሚስት ያገቡ ሰዎችን ይመስላል፡፡ ያለ ዝሙት ምክንያት ሰው ከሚስቱ ቢሰናከል ከእርሷ
በምትበልጥ ሊለውጣትም ቢፈልግ እርሱ በጣም በደለኛ(ኃጢአተኛ) ነው፡፡ ከሀገራቸው የተሻለ ሀገርን የሚፈልጉ ኤጵስ ቆጶሳትም ካሀናትም እንዲሁ ናቸው፡፡ ስለዚህም አውግዘን ለየናቸው፤ይህ ልማድ መጥፎ ነውና፡፡(ፍትሃ ነገስት አንቀጽ 5፡158)፡፡ ይህ በቅዱሳን አባቶቻችን በመጸሐፍ የተቀመጠው ትእዛዝ እና ውግዘት ዛሬ ሲኖዶሱን የሞሉ አብዛኛው አባቶችን
የሚመለከት ነው፡፡ ምክንያቱም አብዛኞቹ በየአህጉረ ስብከቱ የሚገኙ መንበረ ጵጵስናዎች ያለ ሊቀ ጳጳስ ለዓመታት ተዘግተው የሚገኙ ናቸው፡፡ በተጨማሪም አንዱን ስንኳ በወጉ ለማስተዳደር እና ለመመገብ ሳይችሉ አባቶች በድጋሚ ሌላ በርካታ አህጉረ ስብከትን በተደራቢነት በመያዝ ለሌላ ለመታጨት የሚፋጠኑ ናቸው፡፡ ስለዚህ ብፁዓን አባቶች ይህንን የመጽሐፍን ቃል በማዳመጥ እራሳቸውን ከውግዘት ነጻ እንዲያደርጉ በተቀበልነው አደራ እንመክራለን፡፡
ይሁን እንጂ በልዩ ሁኔታ አሁን የተሰጠውን ሲመት በመቃወም ለክፍፍል ምክንያት በመሆን ቅዱስ ሲኖዶስን በማሳሳት ሕዝበ ክርስቲያንን ግራ በማጋባት ላይ የተገኙትን ከዛሬ ጥር 19/2015 ዓ.ም ጀምሮ ከዚህ በታች ስማቸው የተዘረዘሩትን ግለሰቦች
1. ብፁዕ አቡነ አብርሃም የመ/ፓ/ቤ/ክ/ ሥራ አስኪያጅ
2. ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ- የቅዱስ ሲኖዶስ ጸሐፊ
3. ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የጋሞጎፋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ
4. ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል
5. ብፁዕ አቡነ ናትናኤል
6. ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ የሲዳማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ
7. ብፁዕ አቡነ ሄኖክ
8. ብፁዕ አቡነ ድዮስቆሮስ
9. ብፁዕ አቡነ መቃርዮስ
10. ብፁዕ አቡነ ሩፋኤል
እንዲሁም ብቻቸውን አንድ ጳጳስ የሾሙ
11. ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የሲዊድን እና አከባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ የተሸዋሚው
12. ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ
ቅዱስ ሲኖዶስ ስልጣናቸውን ከሊቀ ጵጵስና እስከ ድቁና ያለውን ቤተ ክርስቲያን የሰጠቻቸውን ሥልጣነ ክህነት አንስቶ አውግዞ የለያቸው ሲሆን ከዚህ በኋላ በቀደመ ዓለማዊ ስማቸው አቶ ተብለው እንዲጠሩ ምልዓተ ጉባኤው ወስኗል፡፡
እንዲሁም ሌሎች ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ይህን ቅዱስ ሲኖዶስ ለማውገዝ በጉባኤው የተገኙ አባላት ወደ ማስተዋል ተመልሰው እየፈጸሙ ያሉትን ቤተ ክርስትያንን የመክፈል ተግባራቸውን እንዲያጤኑ እንመክራለን፡፡ ይሁን እንጂ በያዙት አቋም በመጽናት ቤተ
ክርስትያንን የመክፈል ዓላማቸው ላይ የሚጸኑ ከሆነ ከላይ በተጠቀሱት ግለሰቦች ላይ የተላለፈው ቃለ ውግዘት የሚተላለፍባቸው መሆኑን እያሳሰብን በተሳሳተ አቋማቸው ምክንያት ለሚወሰድባቸው ቀኖናዊ እርምት ሃላፊነትን የሚወስዱ ይሆናሉ፡፡
የቅድስት ቤተ ክርሰቲያናችንን ንብረት ለመጠበቅ ሲባል በጊዜያዊነት ከዚህ የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ በኋላ ማናቸውንም በእጃቸው የሚገኙ የቤተ ክርስትያናችንን ንብረት እና ቅርሶች እንዲሁም ለአገልግሎት የሚውሉ ማናቸውንም ንዋየ ቅድሳት ከቦታ ወደ ቦታ እንዳያንቀሳቅሱ እና እንዳያሸሹ ምዕመናን እና በተለያየ እርከን ላይ ያሉ የመንግስት አካላት ተገቢውን ክትትል እና ጥበቃ እንዲያደርጉ እንጠይቃለን፡፡
በመጨረሻም ቅዱስ ስኖዶሳችን ከዚህ በፊት እንደገለጸው በጥር 14/2015 ዓ.ም የተሸሙትን
ኤጵስ ቆጶሳት ወደእየ አህጉረ ስብከታቸው መድቦ ልኮዋቸዋል፡፡ ስለሆነም፡
1. ማኀበረ ካህናት፤ማኀበረ ምእመናን፣ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት እና መንፈሳዊ ማኀበራት በተረጋጋ መንፈስ ሆናችሁ ከዚህ ቅዱስ ሲኖዶስ የሚሰጣችውን መመሪያ በመከተል አስፈላጊውን ዝግጅት በማድረግ በየአህጉረ ስብካታቸው የሚላኩትን ኤጵስ ቆጶሳት በታላቅ ፍቅር እና አክብሮት እንድትቀበሉ እና ለመንፈሳዊ ሕይወታችሁ ማደግ
እንድትተጉ እናሳስባለን፡፡
2. የመንግሥት አካላትም በዚህ ውሳኔ ባኮረፉ ግለሰቦች አነሳሽነት የፖለቲካ ፍላጎታቸውን
በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንዳያንጸባርቁ አስፈላጊውን ጥበቃ እና ክትትል እንዲደርግ
ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡
3. በተወገዙ አባቶች ፈንታ ቅዱስ ስኖዶስ ሌሎች ኤጵስ ቆጶሳትን እስኪሾም ድረስ የየሀገረ
ስብከቶቹ ሥራ አስኪያጆች ተገቢውን የሀገረ ስብከቱን አገልግሎት እንድታስቀጥሉ
መመሪያ እናስተላልፋለን፡፡
ልዑል እግዚአብሔር ሀገራችን ኢትዮጵያን እና ሕዝቦችዋን ይባርክ፡፡
ጥር 19/2015 ዓ.ም አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

Post a Comment

0 Comments